Total Pageviews

Saturday, May 18, 2013

የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ኢንተርኔት ፪


ያለፈው ሳምንት ያነሳሁት ሃሳብ ዛሬም ይቀጥላል፡፡ ኢንተርኔትና የሃገራችን ቋንቋዎች ያላቸው ግንኙነት በጣም አሳሳቢ ነው፡፡ ምናልባትም ነገ ተነገወዲያ ሃገሪቱን ከፍ ያለ ዋጋ ሊያስከፍላት ይችላል፡፡ እኛም ነጋ ጠባ ቋንቋችን፣ የራሳችን የመጻፊያ ሆሄያት ያሉን ማለታችንን ብቻ ሳይሆን ይህንን ከትውልድ የወረስነውን ማንነታችንን ጠብቀንና ቢቻልም አዳብረን ለትውልድ ማስተላለፍ ይገባናል፡፡ ለሀለተኛው ሳምንት ጽሁፌ ስጎሎጉል አንድ ድረ ገጽ አገኘሁ፡፡ ሃገሮች በተለይ በዊኪፒዲያ የእውቀት ባህር ውስጥ የተወከሉበትንና የወከላቸውን ቋንቋዎች ያሳያል፡፡ ካርታውን ከዚህ በታች አድርጌላችኋለሁ፡፡

የራሷ ቋንቋ እና የመጻፊያ ፊደላት ያላት ሃገራችን የተወከለችው በእንግሊዘኛ አንባቢነት ነው፡፡ ምንም እንኳ በዛው ዊኪፒዲያ በአማርኛ ከ10 ሺ በላይ ጽሁፎች ቢኖሩም ሰዎች ለማንበብ የሚሄዱት እንግሊዘኛውን ቅጂ ነው፡፡ አንዳንዴ የሃገራችንን ሰው ታሪክ እንኳ ለማንበብ እንግሊዘኛው እየቀናን ነው፡፡ ይህ በርግጥ በአማርኛ የሚገኙት  ጽሁፎች  እንደ እንግሊዘኛው ቅጅ ሁሉ የተሟላና ዝርዝር አለመሆናቸው ሊሆን ይችላል፡፡ እንዲሆን ማድረግ ግን የኛው ጥረትና ሃላፊነት ነው፡፡ አንዳንዴ ቅኝ ከተገዙ ሃገራት ምን እንደሚለየን አስብና የሚለየን ነገር አለመኖሩ ቢኖር እንኳ የክር ያህል የቀጠነ መሆኑ ይታየኛል፡፡እስቲ ሁለት የዊኪፒዲያ ጽሁፎችን  እናነጻጽር፡፡ የመረጥኩት ራሱ አማርኛን ነው፡፡ ይኸው እንግሊዘኛው...http://en.wikipedia.org/wiki/Amharic_language የአማርኛው ደግሞ ይኸው...http://am.wikipedia.org/wiki/%E1%8A%A0%E1%88%9B%E1%88%AD%E1%8A%9B    በሁለቱ የአንድ ጽሁፎች ሁለት ቅጅዎች ማካከል ያለው ልዩነት የትየለሌ ነው፡፡የእንግሊዘኛው ቅጅ የተሟላ የግስና ሌሎችም ቴክኒካዊ ስርዓቶችን ሁሉ ሲያሳይ አማርኛው ግን የሚያሳየው ታሪካዊ አመጣጡን ብቻ እርሱም አስር መስመር በማይሞላ አንቀጽ ፡፡ የሌሎች ሃገራት ልምድ የሚያሳየው ይህንን መቀየር ይቻላል፡፡ ለምሳሌ የስፓኒሽን የዊኪፒዲያ ታሪክ ብናይ...የስፓኒሽ ዊኪፒዲያ ያኔ ገና በመጀመሪያዎቹ ጨቅላ ዓመታት ላይ ከዊኪፒዲያ ተገንጥሎ ወጥቶ የራሱን ድረገጽ ከፍቶ አሁን ላይ ከዋናዎቹ የኢንተርኔት የመረጃ ምንጭ ሆኖ ይገኛል ለቋንቋው ተናጋሪዎች፡፡  ከዚህ ሌላ እኔ በግሌ ያስደነቀኝ በስፔን የሚገኘውና በካታላን ህዝቦች የሚነገረው የካታላን ቋንቋ ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቋንቋ የበለጠ የጽሁፍ መጠን በዊኪፒዲያ ላይ ማስመዝገቡ ነው፡፡ ይህ ከ15 ሚሊዮን የማይበልጥ ተናጋሪ ያለው ቋንቋ ከ62 ሚሊዮን የበለጠ ተናጋሪ ያለው አማርኛ  ጋር ያላቸው ልዩነት አይመጣጠንም፡፡ የካታላን ቋንቋ በስሩ ከ402 ሺ የበለጡ ጽሁፎችን ሲይዝ የአማርኛ ቋንቋ ግን 12 ሺ ያህል ጽሀፎችን ይዟል፡፡ ይህም 12ሺ ጽሁፍ ከ6 ባልበለጡ አስተዳዳሪዎች ኤዲት የተደረገ ነው፡፡ ይህ ከፍተኛ የመጠን ልዩነት ከየት የመጣ ነው? የካታላን ቋንቋ በሶስት ሃገሮች ከ15 ሚሊዮን ባነሰ ህዝብ ይነገር እንጂ ከሌሎች በተለይም ከስፓኒሽ ተናጋሪዎች ጋር ያላቸው ግጭት ለዚህ ልዩነት ከፍ ያለ አስተዋጽኦ ሳያደርግ አይቀርም፡፡ በስፔን ስር የሚገኙ ካታላን ተናጋሪዎች የሚገኙበት ክልላዊ መንግስት ለቋንቋው ማደግ ከፍ ያለ አስተዋጽኦ ሳያደርግ አይቀርም ይባላል፡፡ እንደሚባለው ክልላዊ መንግስት ለዚሁ ብቻ ሲባል ቋንቋው በኢንተርኔት ላይ ያለውን አሻራ የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች ላይ አትኩሮ የሚሰራ ተቋም አለው፡፡ በዚህም ምክንያት አሪፍ የተባሉ ስነጽሁፎች፣ ቲያትሮችና መጻህፍት ወደ ካታላን ቋንቋ ተተርጉመዋል፡፡ ካታላን ቋንቋ ለካታላን ህዝቦች የማንነታቸው አንድ መሰረት ነው፡፡ ለዚህም ነው በመንግስት ደረጃ ቋንቋውን ለማሳደግ የሚደክሙት፡፡ አማርኛ ወይንም ሌላውም የሃገራችንን ቋንቋ በሌላ ወገን እንደምሳሌ ዊኪፒዲያን ወሰድነው እንጂ  በኢንተርኔት ላይ ያለው አሻራ ኢምንት ነው፡፡ በመሆኑም የሚከተሉትን መፍትሄዎች ብንጠቀም ችግሩን ልንቀርፍ እንችላለን ብዬ አስባለሁ፡፡                
1.      ሃላፊነቱ ያለባቸው የትምህርት ተቋማት፣ የባህል ሚኒስተር፣ የማስታወቂያ፣ የመገናኛና ኢንፎርሜሽ ሚኒስትር መስሪያቤቶች እንዲሁም ሌሎች የመንግስት  አካላት የተሰጣቸውን ሃላፊነቶች በይበልጥ እንዲወጡት...ካልተሰጣቸውም በአዋጅ ስራቸውን በማሻሻል እንዲያከናውኑት ማድረግ፡፡
2.     ሃገር የምታድገው በንግድና ኢንደስትሪ ብቻ አይደለምና ዜጎች ለሃገራቸው ባህልና ቋንቋ ቅድሚያ እንዲሰጡ ማስተማር
3.     በተለይ ኢንተርኔትን በተመለከተ ግለሰቦች ከመንግስታት የበለጠ ጉልበት አላቸውና ተማርን ነቃን የምንል ነገ የምትተርፍ ሃገር እንድትኖረን መጣር ይገባናል፡፡
     
      ለምሳሌ ጥቂት ማድረግ የምንችላቸው ጥረቶች ይኖራሉ፡፡ የስፓኒሽ ዊኪፒዲያ ከዋናው ዊኪፒዲያ ጋር በነበረው ጠብ ምክንያት ተለያይቶ ወጥቶ የስፓኒሽ ሃገራዊ እውቀቶችና ባህል ላይ የሚያተኩር የራሱን Enciclopedia Libre Universal en Español የተሰኘ የእውቀት ባህር ከፍቷል፡፡ ስለዚህ እኛም ወይ በዋናው ዊኪፒዲያ ስር ወይንም ይበልጥ በተደራጀና ቁጥጥር ባለው  ሁኔታ የራሳችንን ኢንሳይክሎፒዲያ መፍጠር እንችላለን፡፡ በመጻህፍት ያከማቸነውን እውቀት መቼም ዘመኑ ነውና ለሁሉም ተደራሽ ማድረግ ይገባናል፡፡ይህንን ለማሳካትም የተጀመሩ ጥረቶችን ለመደገፍ ሊቋቋም የታሰበ ፕጀሮጀክት አለ፡፡ የፕሮጀክቱ የመጀመሪያ ሃሳብ የወል ጥረት ውጤት የነበረው wikipedia.org ላይ በተጀመረው የአማርኛ ፕሮጀክት ስር በተደራጀ ሁኔታ በበጎ ፍቃደኞች የሚተረጎሙና የሚጻፉ ወጥ ጽሁፎችን ማዘጋጀት ነበር፡፡ ይህንንም ለማሳካት  ኢትዮጵያውያን በወደዱትና በሚያውቁት የእውቀት መስክ የተመረጡ ጽሁፎችን በማዘጋጀት በተለይ የሃገር ውስጥ ተማሪዎችን ጠቅላይ እውቀት በእናት ቋንቋቸው እንዲያገኙ ማድረግ ነበር፡፡ ይሁንና በተለይ ከቅርብ ጊዜ ጀምሮ ዊኪፒዲያ ድረገጽ እያስተናገደ ካለው ትችት አንጻር ከዛ የሚገኙ ጽሁፎችን በሙሉ መጠቀም አስቸጋሪ ነው፡፡ ለማንኛውም አንድን ድረገጽ ከፍቶ ማስተዳደር ያህል ቀላል ሆነው ይህ ፕሮጀክት አሁንም ከመንግስት ከመንግስታዊ ካልሆኑና ከግለሰቦች በተወጣጣ ቡድን እየተመራ ታሪክንና ሳይንስን፣ ጥበብንና መረጃን በሃገር ቋንቋ ለሃገር አዳጊ ልጆች ማቅረብ እንችላለን፡፡ ምናልባት በዚህ ሃሳብ ጉዳይ ላይ የተለየ፣ ተጨማሪ ወይንም መሳተፍ የሚፈልግ በኢሜል አድራሻዬ feruzj30@gmail.com በኩል ሊያገኘኝ ይችላል፡፡ ከአባቶቻችን የተቀበልነውን ቋንቋ መጠበቅ ብቻ ሳይሆን ማሳደግና ለትውልድ ማስተላለፍ ግዴታችን ነው፡፡ ይብቃኝ ሃሳቦቻችሁንና ጥያቄዎቻችሁን እጠብቃለሁ፡፡ አመሰግናለሁ....ኢትዮጵያችን ለዘላለም ትኑር!


ጸሃፊው ፌሩዝ ጀማል በሸገር ኤፍ.ኤም 102.1 ሬዲዮ በ IT, ድምጽ ላይብረሪና ፕሮግራም ትራፊክ ሃላፊነት ይሰራሉ፡፡ ጸሃፊውን ለማግኘት በፌስ ቡክ ገጻቸው https://www.facebook.com/feraj?ref=tn_tnmn  በኢሜላቸው feruzj30@gmail.com መጠቀም ይቻላል፡፡


Saturday, May 11, 2013

የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ኢንተርኔት




ዓለም ከ50 ዓመታት በኋላ እንዴት ትሆን?..ይሄ ገሎበላይዜሽን (Globalization) አሁን የምናውቃትን ዓለም የፈጠረውን የዘር፣ የቋንቋ፣ የባህልና ምናልባትም የቀለም ልዩነቶች እያደበዘዛቸው ነው፡፡ በአንጻሩም የአንድ ዓለም…የአንድ ህዝብ…የአንድ ባህል ፍልስፍና እየጠነከረና እየደመቀ ነው፡፡ ይኼም በየቀኑ ኢንተርኔት ስጎለጉል ይበልጥ ይታየኛል፡፡ ኢንተርኔት ሙሉ ለሙሉ ማለት ይቻላል በእንግሊዘኛ ተጀምሮ አሁን ላይ ወደ ሌሎች ቋንቋዎች እየተስፋፋ ቢመጣም አሁንም በ 'ሌሎች' ቋንቋዎችና በእንግሊዘኛ መሃል ያለው የመጠን ልዩነት ግዙፍ ነው፡፡ በመላው ዓለም ከሚነገሩ 6000 በላይ ቋንቋዎች እንግሊዘኛ የአንበሳውን ድርሻ ይዟል በኢንተርኔት፡፡ ለነገሩ መጀመሪያ እኒህ ከ6000 የበለጡ የንግግር ቋንቋዎች የጽሁፍም ቋንቋዎች አለመሆናቸውን ልብ ማለት ያሻል፡፡ ራሳቸው የቋንቋ ባለሙያዎችም ቢሆኑ በቁጥሩ ዙሪያ የተስማሙበት አይደለም፡፡ ይሁንና እኛ ለጨዋታችን እንዲረዳን ከ6000 ቋንቋዎች ግማሹ ያህል የጽሁፍ ቋንቋም ናቸው ብለን እናስብ፡፡ በነገራችን ላይ አንድ ቋንቋ የጽሁፍም ለመሆን የግድ የራሱ ፊደላት እንዲኖሩት አያስፈልግም፡፡ ለምሳሌ ከሃገራችን እንኳ የላቲን ፊደላትን የሚጠቀሙትን የኦሮምኛ እና የሶማሊኛ ቋንቋዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ወደ ኢንተርኔታችን እንመለስ፡፡ ከነዚህ ከ3000 ሺ የበለጡ  ቋንቋዎች እንግሊዘኛ 57 በመቶ ያህሉን ድርሻ ይዟል፡፡ ከዚህ የተረፈውን ደግሞ ራሺያን፣ ጀርመን፣ ስፓኒሽ፣ ቻይኒዝ፣ ፍሬንች፣ ጃፕኒዝ…እያልን መቀጠል እንችላለን፡፡ ቀጥለን ቀጥለን ግን 2900 በላይ የአለም ቋንቋዎች ከ0.1 በመቶ በታች ድርሻ ነው ያላቸው በኢንተርኔት ውስጥ፡፡ ከነዚህ መሃል አማርኛ፣ ኦሮምኛ፣ ትግረኛና ሌሎችም የሃገራችን ቋንቋዎች ይገኛሉ፡፡ ይህ የእንግሊዘኛ ገንኖ መውጣት አሁን አሁን ላይ እየቀነሰ እየመጣ ቢሆንም ያለው ድርሻ ግን እንዲሁ በቀላሉ የሚነጠቅ አይሆንም፡፡ 
የአለም ቋንቋዎችና ኢንተርኔት - ከዊኪፒዲያ የተወሰደ



እንደ http://www.internetworldstats.com (http://www.internetworldstats.com/stats7.htm) ከሆነ የእንግሊዘኛ ተናጋሪዎች በ10 ዓመታት ማለትም ከ2000 የፈረንጅኛው የዘመን ቆጠራ እስከ 2011 ድረስ ያሳዩት ኢንተርኔትን የመጠቀም እድገት ያን ያህል የሚጋነን ባይሆንም ቋንቋው በኢንተርኔት ውስጥ ያለው መጠን አሁንም እያደገ ነው፡፡ ሃገሮች ምንም እንኳ ብሄራዊ ቋንቋቸው እንግሊዘኛ ባይሆንም የሚፈጥሩት ድረገጽ ግን እንግሊዘኛ ነው፡፡ በሃገራችን የሚገኙትን ትልልቅ የምንላቸውን ድረገጾች ብናይ እውነቱ ግልጽ ይሆናል፡፡ www.shegerfm.com , www.diretube.com, www.ethiotelecom.et (በተለይ ይኼኛው ሁለቱንም ቋንቋዎች ቢይዝም የመነሻ (default language)ግን እንግሊዘኛ ነው፡፡) www.nazret.com, www.ezega.com , www.ethiopianreview.com , www.tadias.com ፣ www.2merkato.com. እነዚህ ድረገጾች በዋነኝነት የተመሰረቱት ለኢትዮጵያውያን ሆኖ…አማርኛም የሃገሪቱ ብሄራዊ ቋንቋ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ…የምናገኛቸው በእንግሊዘኛ መሆኑ አስገራሚ ይመስላል፡፡ ከዚህ ሌላ ደግሞ የመንግስት ድረገጾችን ብናይ  በአብዛኛው በተለይ አሁን አሁን አማርኛ የመነሻ (default language) እየሆነ ነው፡፡ ድረገጾቹ አማርኛን በመነሻነት ይዘው ትግረኛን፣ ኦሮምኛን እና እንግሊዘኛ ቅጂዎችንም አቅፈዋል፡፡ ለምሳሌ http://www.ethiopia.gov.ethttp://www.moe.gov.et, http://www.mofed.gov.et, http://www.moh.gov.et መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከነዚህ ውጭ በመነሻነት እንግሊዘኛን የሚጠቀሙ የመንግስት ድረገጾችም አሉ ከነዚህ ውስጥ http://www.tourismethiopia.gov.et, ዋነኛው ነው፡፡ ከመንግስት ድረገጾች ውጭ የዜና ፖርታሎች ለምሳሌ አዲስ አድማስ እና ሪፖርተር ጋዜጣዎችም በአማርኛ የተዘጋጀ ድረገጽ አላቸው፡፡ ይህ በሃገር ውስጥ ያለውን ሁኔታ ሲያሳይ ከውጭ ሃገር ድረገጾች በጣም ትኩረቴን የሳበውን ላጫውታችሁ፡፡ ሁላችንም የምናውቀው የኢንተርኔት ኢንሳይክሎፒዲያ www.wikipedia.org በአማርኛ ከ10 ሺ በላይ ጽሁፎችን ይዟል፡፡ ምናልባትም ይህ ቁጥር በአጠቃላይ በሃገር ውስጥ ያለውን የአማርኛ የኢንተርኔት ጽሁፍ መጠን ሳይበልጥ አይቀርም፡፡ በአፋን ኦሮሞና ትግረኛ ከመቶ በላይ ጽሁፎች ይገኛሉ፡፡ከዚህ ሌላ ዊንዶውስ 7ና 8 ከማይክሮሶፍት ካምፓኒ፣ አብዛኞቹ የመሰረተ-ሊነክስ ኦፐሬቲንግ ሲስተሞች  ለአማርኛንና ኦሮምኛን ድጋፍ ያደርጋሉ፡፡ ለምሳሌ ኡቡንቱ ኦፕሪቲንግ ሲስተም ኮምፒውተራችንን በአማርኛ እንድንጠቀም ያስችለናል፡፡ ኧረ እነ ጉግልም የአማርኛ ሰርች ገጽ አላቸው፡፡ ይሁንና አብዛኛው ኢንተርኔትን በኢትዮጵያ ቋንቋዎች የመጠቀም እድሉን እያመቻቹ ያሉት ግን ሃገር ውስጥ ያለነው ወይንም ጉዳዩ በጣም የሚመለከተን አካላት አይደለንም፡፡ ወይ የንግድ ድርጅቶች ወይም ለትርፍ ያልተቋቋሙ እንደ ዊኪፒዲያ ያሉት ናቸው፡፡ በሌሎች የኢትዮጵያ ቋንቋዎች መረጃ ከኢንተርኔት ላይ የማግኘት ነገርንማ አናስበው፡፡ ጠቅላላ መረጃን በተመለከተ አሁን ያለው የሃገራችን ቋንቋዎች ተሳትፎ ብዙም የሚያወላዳ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ማን ሃላፊነቱን እንደሚወስድ ግልጽ አለመሆኑ አሳሳቢ ነው፡፡ በሌሎች ሃገራት ለምሳሌ በስፔንና በስፓኒሽ ተናጋሪ ሃገራት እንዲሁም በፊሊፒንስ ቋንቋቸው በተለይ በኢንተርኔት ላይ ያለው ምልክት አነስተኛ መሆኑ አሳስቧቸው የተቋቋሙ ማህበራት ይገኛሉ፡፡ በአማርኛ ማንበብ ብቻ ሳይሆን በተመቻቸ ሁኔታ ኢንተርኔት ላይ በአማርኛ መጻፍን መጀመር አለብን፡፡ ለዚህም የአይቲ ባለሙያዎች ሃላፊነት ይኖርባቸዋል፡፡ ከዚህ ሌላ በዚሁ በኢንተርኔት ውስጥ የኢትዮጵያውያን ጥበብና እውቀት በአግባቡ አለመወከሉም ሊያሳስበን ይገባል፡፡ የአለምን ታሪክ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያንም ታሪክ ከኢንተርኔት በአማርኛ ማግኘት ያስፈልገናል፡፡ ዜናና መረጃ ብቻ ሳይሆን ሂሳብን፣ ሳይንስንና መማሪያ ጽሁፎች በአማርኛ ልናገኝ መብታችን፣ ይህንኑ ማመቻቸትና ለትውልድ ማስተላለፍ ሃላፊነታችንም ነው፡፡ ያለበለዚያ ታሪካችን፣ ባህላችንና ማንነታችን በቀላሉ ይዋጣል፡፡አንዳንድ የቋንቋ ባለሙያዎች ከአለም ቋንቋዎች ግማሹ ያህል በ2050 ይጠፋሉ ብለው ያምናሉ፡፡ መጀመሪያም ይህ የነበረ ችግር ቢሆንም ኢንተርኔት ደግሞ ነዳጁን አርከፍክፎበታል፡፡ ስለዚህ ከመንግስትም ሆነ ከመንግስት ውጭ የሃገራችን ቋንቋዎች ትኩረት ይሰጣቸው! ለዚህ የመረጃ ዘመን ይብቁ እላለሁ፡፡ ሳምንት መፍትሄ የምለውን ይዤ እመጣለሁ፡፡ 
ጸሃፊው ፌሩዝ ጀማል በሸገር ኤፍ.ኤም 102.1 ሬዲዮ በ IT, ድምጽ ላይብረሪና ፕሮግራም ትራፊክ ሃላፊነት ይሰራሉ፡፡ ጸሃፊውን ለማግኘት በፌስ ቡክ ገጻቸው https://www.facebook.com/feraj?ref=tn_tnmn  በኢሜላቸው feruzj30@gmail.com መጠቀም ይቻላል፡፡

Friday, May 3, 2013

ለማንነታችን መገለጫዎች ክብር እንስጥ!!!



እኛ ኢትዮጵያውያን ከአለም በዚህ ነገር አንደኛ ምንናም እያልን የምንኮፈስባቸው ብዙ መገለጫዎች ያሉን ህዝቦች ነን፡፡ የአለም ህዝብ በአድናቆት ያጨበጨበላቸው የጥንት ስልጣኔዎቻችን አሻራ ያረፈባቸው አክሱም፤ላሊበ፤ነጃሺ መስጊድና የመሳሰሉት፡፡በብዝሀ ህይወት ሀብታቸው የአለም ቁንጮ ያደረጉን እን ሰሜን ፣አዋሽ ፤ባሌ ተራሮች ፤ኦሞ ፤ነጭሳርና ጋምቤላ ብሄራዊ ፓርኮቻችን እና በውስጣቸው የሚገኙት እነ ዋልያ፤ቀይ ቀበሮ፤ሳላህ፤ኒያላ የመሳሰሉት ብርቅዬ እንስሳት፤የቱሪስት መንጋጊያ የሆኑት እነ አዋሳ ፤ጣና ፤ላንጋኖ፤ሻላ እና አቢያታ ሀይቆቻችን በእርዝመታቸው በአለም ከሚጠቀሱ ወንዞች መካከል እነ አባይ፤ባሮ፤አዋሽ፤ጊቤ፤ዋቢ ሸበሌ የመሳሰሉት ታሪክ ሲያወሳቸው የኖሩት የነገስታቶቻችንና የፈላስፎቻችን ስሞች እነ ሚንሊክ፤ቴዎድሮስ፤፤ምንትዋብ፤ካሌብ፤ዘረያቆብና ሱሲኒዮስ፡፡
የአለም ዝቅተኛው ስፍራ ዳሎል ፤ኤርታሌ ፤የሉሲ መገኛ ሃዳር …..እረ ስንቶቹ ተጠቅሰው ያቻላል፡፡በዘፈን የምናውቃቸው እነ ባቲ፤አምባሰል ፤መቅደላ፤ገራዶ፤…እነዚህ ሁሉ ድንቅ ስሞች በሞሉባት ሀገር ….Network café, Dallas café, Denver, lime tree café, Boston day Spa, Jolly bar, purple café, liquid lounge, flirt lounge, platinum, H20, Faranite, Stockholm, Amsterdam…እረ መአት አሉ ፤(እነ ሱባ ላውንጅ ፤እን ጃዝ አምባ፤እነ ቃተኛ፤እንጎቻ ፤ላሊበላ ፤እክሱም ሬስቶራንቶች ፤ሙልሙል ዳቦ የመሳሉትን ስያሜዎች ሳላደንቅ አላልፍም )፡፡
እረ ግን ምነው የኛ ስሞች የማይመጥኑ ሆነው ነው?....ወይስ??? በጣም የሚገረመኝ ደግሞ የባህላዊ እቃ መሸጫዎቻችን ስያሜዎች ናቸው …ፕሪቲይ ጥበብ፤ፐርፌክት የባህል ልብሶች መሸጫ፤ቴክሳስ የባህል እቃዎች ምናምን (እነ እቴጌ ጥበብ፤ጋሙ የባህል ልብስ ፤አምባሰል የመሳሉትን አሁንም ሳላደንቅ አላልፍም)፡፡
የባሰ የሚገርመውና የሚያሳፍረው ነገር ደግሞ …የፊልሞቻችን ነው፡፡በአማርኛ ፊልም ሰርቶ ርዕስ በእንግሊዘኛ እስቲ አሁን ምን ይሉታል ????... ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህል(መቼም ተሰልፌ ባላያቸውም ተዋንያኖቹ ሀበሾች ስለሆኑና “ምርጥ የአማርኛ ፊልም” ብሎ ከሚጀምረው ማስታወቂያቸው የአማርኛ ፊልም መሆናቸውን አልጠራጠርም) City boy, Mr X, FBI, Honeymoon, Surprise, Made in China…ደሞ አሉ እንጂ shefu, mechaniku (ወይ ሙሉ በሙሉ እንግለዘኛ አልሆኑ ወይ አማርኛ አልሆኑ በቃ ጉራማይሌ ) እረ እንደው ስንቱ ተጠርቶ ስንቱ ይተዋል፡፡ እስቲ አሁን ከሀኒሙን እና ከጫጉላ የትኛው ያምራል??? ከሲቲ ቦይዝና ከከተማ ልጆችስ???...ፍርዱን ለናንተው፡፡
ለልጆቻችን እያወጣን ያለው ስምስ …Nancy, Barabara, Robert, Terry, Obama, mattew ምናምን??? እናትና አባቶቻቸው thank you, still, stupid ከሚሉት ከአስር ያልበለጡ እንግሊዘኛ ቃላት ውጪ የማይችሉ ህጻናት እንግሊዘኛ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸው እስኪመስል ድረስ አማርኛ እየረሱ ነው ....ይሄስ ምን ይሉታል???  አማርኛ መናገር የሚያስቀጣባቸው ት/ቤቶችስ እንዳሉ ታውቃላቸውሁ? እንዴታ እንኳን እኛ መንግስትም ያውቃል አትሉኝም፡፡
እንደው ለነገሩ እነዚህን ጠቃቀስኩ እንጂ ስንት አለ እኮ በየመንደሩ ኦባማ በለጬ፤ቦልት በለጬ፤ አርሰናል አወዳይ፤ ኦፕራ ምርጥ የጉራጌ ጫት ምናምን ጉድ እኮ ነው እነ ኦባማ፣ ቦልትንና ኦፕራን የመሳሰሉ የአለም እንቁዎች ለጫት መጠሪያነት ??? አንዱ ምን እንዳለኝ ታውቃለችሁ፡፡እነዚህን ስሞች እኮ የሚሰየሙት ቃሚዎቹ ቅመው እንደነሱ እንዲያስቡ ነው፡፡ባለ መቶው ቦልት በለጬ ደግሞ አለኝ ከ9 ሰከንድ ባነሰ ያመረቅናል(ቦልት መቶ ሜትሩን ከ 9 ሰከንድ በታች እንደገባው ማለት ነው) ጉድ አኮ ነው!!
ዳላስ እንጀራ ፤ካሊፎርኒያ ድፎ ዳቦ፤ሎስአንጀለስ በርበሬ፤ቤጂንግ ቁርጥ ቤት፤ሎንደን ጠላ ቤት ፤ዲሲ ባልትና የሚሉ ስያሜዎች በቅርቡ ማንበባችን አይቀርም፡፡እስካሁን ላለመኖራቸውም እርግጠኛ አይደለሁም፡፡
ጓዶች አማርኛችን ሀብታም እኮ ነው፡፡ሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች በኛ ብቸኛ ፊደል ይኮራሉ እኮ፡፡ታዲያ እኛ ወዴት እየሄድን ነው? ለነገሩማ መሪዎቻችንስ አሻራ የምትል ጥፍጥ ያለች አማረኛ ቃል እያለች (legacy), በለውጥ ፋንታ (transformation) እያሉ የሚያደነቁሩን፡፡ በሌላውማ እንዴት ይፈረዳል፡፡
ለነዚህ የአሰያየም ችግሮች ሰዎች የተለያዩ ምክንያቶችን ያቀርባሉ፡፡የወጣቱን ትኩረት ለመሳብ ፤የውጪ ዜጎችን ቀልብ ለመስረቅ የመሳሰሉት ፡፡እንደ እኔ ግን ወጣቱን የራሱን ባህል ፤ማንነትና  ብሄራዊ ስሜቱን ትቶ የውጪ ባህል ናፋቂ እንዲሆን እያደረግን ነው ትኩረቱን የምንስበው? ኧረ ጥሩ አድርገን ከሰራነው እኮ የወጣቱንም ሆነ የውጪ ጎብኚዎችን የምንስብባቸው ስንት ነገሮች አሉን፡፡በጃሉድ “የእርግብ አሞራ” ያልጨፈረ ወጣት አለ እንዴ? የእርግብ አሞራ እኮ ባህላዊ የህዝብ ዘፈን ነው፡፡ አሪፍ አርጎ ስለሰራው ግን የወጣቱን ቀልብ መሳብ ችሏል፡፡
ያደጉት ሀገራት ያደጉት እና እዚህ የደረሱት እኮ የራሱን ትቶ የሰው ናፋቂ የሆነ ትውልድን ይዘው አይደለም፡፡ይልቁኑንስ ለባህላቸው ፤ለማንነታቸውና ለብሄራዊ ስሜታቸው ክብር ሠጥተው እንጂ፡፡ ታዲያ እኛስ ክብር የምንሰጠው ነገር የለንም ወይስ???.... ጎበዝ እናንተው ፍረዱት!







kuku. A eb እዚሁ ፌስቡክ ላይ በመጻፍ ይታወቃሉ! በሙያቸው ጠበቃ ሲሆኑ የሚያነሷቸውን ማህራዊ ሃሳቦች የሚተቹበት ገጽ አላቸው….እነሆ አድራሻው!  https://www.facebook.com/kuku.eb ኢሜላቸውን ከፈለጉም እነሆ! kuku.eb@facebook.com

Saturday, April 27, 2013

“Don’t Judge a book by its cover “አሉ ፈረንጆቹ ሙድ ሲይዙብን



“Don’t Judge a book by its cover “አሉ ፈረንጆቹ ሙድ ሲይዙብን
ፍተሻ አለም ላይ
ፍተሻ ለግል ፤ለማህበረሰብ እና ለሀገር ደህንነት ያለው አስተዋፅዎ እጅግ በጣም ከፍተኛ መሆኑን ሁላችንም የምንስማማበት ይመስለኛል፡፡ከደህንነት ጥበቃ ማነስ አንጻርም የስንቱ ህይወት በከንቱ እንደቀረም የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡ለዚህም ነው ሀገሮች ከምንም በላይ ለጥበቃቸው ትኩረት ሰጥተውና ዳጎስ ያለ በጀት መድበው የሚንቀሳቀሱት፡፡
ፍተሻ እኛ ሀገር
ስለፍተሻ ጉዳይ ሳስብ በአየር መንገድና በከተማችን በሚገኙ ትላልቅ ሆቴሎች ያለው አስተማማኝ የጥበቃና የፍተሻ ሁኔታ በጣም ያረካኛል፡፡ሁሉም ለራሱ ደህንነት ሲል እኩል የሚፈተሽበት፡፡ ያውም በደስታ በነጻነት፤ ያለፍርሀትና የደህንነት ስጋት ሳያጋጥመን ለመዝናናት፤ለመስራት ብሎም ለመጓጓዝ፡፡ነገር ግን……….ነገር ግን ዐረፍት ነገሩን አፍራሽ ያደርገዋል ተብለን አይደል የተማርነው ፡፡
እና እኔም ነገር ግን ብያለሁነገር ግን በፍተሻ ቦታዎች ላይ( በአንዳንድ ሆቴሎች፤ባንኮች ፤የመዝናኛ ስፍራዎች፤ሲኒማ ቤቶችወዘተ) እየደረሰብን ያለው መገለልና መድሎ ይቁምልን ነው፡፡እንዴ ሰው ባገሩ እንዴት ..እንዲህ አይነት መድሎ ይደርስበታል፡፡ቆይ እኔ ምለው ለሀገር ደህንነት ስጋት መሆን ያለበት ኢትዮጵዊ ነው ወይስ የውጪ ዜጋ(እዚህ ጋር ልብ ሊባል የሚገባው ሁሉም የውጪ ዜጋ የሀገር ስጋት ነው፤ኢትዮጵያዊ ደግሞ የሀገር ስጋት ሊሆን አይችልም የሚል የጅምላ ድምዳሜ ላይ አልደረስኩም)፡፡ ነገር ግን ቀለሙ ነጭ ስለሆነ ብቻ ከስጋትና ከጥርጣሬ ነጻ መሆን አለበት ወይ? እንደኛ ቀለሙ ስለጠቆረ ደግሞ(ያውም በገዛ ሀገሩ) መጠርጠር አለበት ወይ ነው ጥያቄዬ? “ባለቤቱ የናቀውን አሞሌ ባለእዳ አይቀበለውምአይደል ተረቱ:: ቆይ እርስ በእርስ ከተጠራጠርን ማን ሊያምነን ነው??? ከሀገሬ ወጣ ስል ለሚያጋጥመኝ የተንዛዛ ፍተሻ አሪፍ መጽናኛ አለችኝ እንዴ የኔው የራሴ ሰዎች እንደዚያ አገላብጠው ከፈተሹኝ ባዕዶቹማ እንዴት አይበረብሩኝ? ብዬ እፅናናለሁ፡፡
ከሁሉም ግን ግርም የሚለው ነገር፡፡በገዛ ሀገራችን አንድ አይነት ቦታ ላይ ነጮቹ ሳይፈተሹ ሲገቡ እኛ አንዳንዴ ስብዕናችንን በሚፈታተን መልኩ የምንበረበረው ነገር ነው፡፡አንዳንዴ ንዴታችሁ ብልጭ ብሎባችሁ ለምን የውጪ ዜጎቹ እንደማይፈተሹ ጥያቄ ካነሳችሁማ በቃ ጭራሽ አትገቡም ልትባሉ ሁሉ ትችላላችሁ፡፡
አንዴ እንዲህ ሆነ…
አንድ ስብሰባ ነገር ነበረችኝ፡፡ቦታው በከተማችን ካሉት ትላልቅ ሆቴሎች በአንዱ ነው፡፡ የኔ ስራ ለውይይቱ መነሻ ሀሳብ የምትሆን ጽሁፍ ቢጤ ማቅረብ ነበር፡፡በወቅቱ ቀጫጫ ቤጤ ነበርኩና ያው እንደሚታወቀው እኛ ሀገር ለመከበርና አንቱታን ለማግኘት ስጋ፤ ቦርጭና አለባበስ ግድ ይላል፡፡ያኔ ጥሩ ለብሻለሁ ስጋና ቦርጭ ግን አልነበረኝም ፡፡ማህበረሰባችን ደግሞ እንደ ፋሲካ በግ ከላይ አይቶ ነው የሚገምትህ ምክንያቱም “Don’t Judge a book by its cover “ የምትለውን አባባል አያርፍማ፡፡
እናም ትንሽ አርፍጄ ነበርና በር ላይ ስቻኮል ለፍተሻ ሁለት የሆቴሉ ጠባቂዎች መኪናችንን ያስቆሙናል፡፡እሺ ብለን አቆምንና መኪናችንን አገላብጠው በረበሯት፡፡ሞተር መፍታት ነው የቀራቸው፡፡ጋራዥ ነው እንዴ እስክንል ድረስ፡፡ይሄም አልከፋንም በጄ ብለን ነበር፡፡እኔም ሾፌሩም ውረዱ ተባልን፡፡ወረድን፡፡እኛንም ልክ እንደመኪናዋ በረበሩን፡፡ ኧረ ሞተር እንዳይፈቱብን ተባብለን ተሳሳቅንም ተሳቀቅንም፡፡
ወዴት ነውየሴቷ ጥበቃ ጥያቄ ነበር
ይቅርታ የኔ እህት ሆቴል መስሎኝወዴት ነው ተብሎ ይጠየቃል እንዴ ..? ትንሽ ጥያቄው አናዶኝ ነበር
ማነሽወዴት እንደሆነ ካልተናገርሽ አትገቢም” …በቁጣና በገልምጫ
ሾፌሩ ትንሽ እንደመናደድ እየቃጣው ስለኔ መናገር ጀመረ
አይመለከትህም እሷ ትናገር…”
ስነ ስርአት….” አለ በንዴት ሾፌሩ
በዚህ መሀል አምስትና ከዛ በላይ የሚሆኑ ፈረንጆችን የጫነች ሚኒ ባስ ያለ ክልከላና ያለ ጠያቂ ሰተት ብላ ገባች….አይኔን ማመን ነው ያቃተኝ፡፡ማንም የተናገራት የለም፡፡ በዚህ ቢበቃ እኮ ጥሩ ነው፡፡ ጀርባቸው ላይ አነስ ያለች መኪና የምትጭነውን ያህል ትልቅ ቦርሳ፤ የስፖርት እንዲሁም የሙዚቃ መሳሪያዎችን ያየዘ ሌላ ቦርሳ የተሸከሙና ተራራ ወጪ የሚመስሉ ሶስት ፈረንጆች ቀጥ ብለው ገቡ፡፡ወዴት ነው? እንዴት ነው?ማናችሁ? ያላቸው ሰው አልነበረም፡፡
ይሄኔ ሾፌሩ መሳደብ ጀመረእኔ በቃ የምናገረው ነገር ግራ ገብቶኝ ቆሜያለሁ፡፡በዚህ መሀል ወንዱ ጥበቃ መጣና ከኛ ጋር ክርክር ጀመረ፡፡
የኔ እመቤት የስብሰባው ሰዓት እረፍዶብኛል እባክሽ በኋላ እንነጋገራለን ..አሁን ልግባበጣም በትግስትና በአክብሮት ነበር የጠየኳት፡፡አሻፈረኝ አለች፡፡
እንድዉም መኪናውን አውጣ ምናምን መባል ተጀመረአሁን እኔም ተናደድኩ……ስብዕናዬን ተፈታተኑኝ፡፡ወንዱ ጥበቃ በመሀል መታወቂያ አለ፡፡
መታወቂያን ለሁለታቸሁም አልሰጥም…”አልኩና ስብሰባውን የሚያስተባብረውን አለቃዬን ከውስጥ በስልክ ደውዬ ጠራሁት ፡፡
አለቃዬ ሲሮጥ መጣ ….ዝንጥ ያለ ሱፍ ለብሷ ፤ቦርጭም ስጋም አለው፡፡እኔ ለራሴ ቀጫጫምንም የሌለኝ፡፡
እሱ መምጣቱን ሲያዩ
ወንዱ ጠባቂበአንዴ አከበረኝ አንቺ ምናመን ሲል እንዳልነበርበቃ አሁን እርሶ ይግቡ በኋላ እንነጋገራለንምናምና ማለት ጀመረ ማማን አቃተኝሳኩበት ፤አፈርኩበት፤ቅድም ፍተሻው ላይ የተሳቀኩት ሳያንስ ለሰውዬው አስተሳሰብ እኔ ተሳቀኩኝ
አልገባም አልኩኝአለቃዬኧረ ሰአት እረፍዷል ..እንግዶች እየጠበቁ ነው ምናምንአለ፡፡
አልገባም….መግባት የምፈልገው በራሴ ነው በአንተ ወይም በእገሌ አይደለም፡፡ሀላፊያቸው ይጠራልኝና እሱን አናግሬ እገባለሁከነሱ ጋር በኋላ እነጋገራለሁ አልኩኝ፡፡
ለማንኛሁም ሀላፊው ተጠራ አናገርኩት ገባሁ ስወጣ ግን እነዛ የጥበቃ ሰራተኞችን ዝም ብዬ ላልፋቸው አልፈለኩም ፤ስነምግባሩም አይፈቅድልኝም፡፡ሃላፊያቸው መጣ ፤ይቅርታ ጠየቀኝ፤እነሱም ተጠሩ ይቅርታ ጠየቁ፡፡ይቅርታቸው ግን አልካሰኝም፡፡አላስደሰተኝም፡፡እነዚህ ጥበቃዎች መማር አለባቸው ብዬ አሰብኩኝ፡፡ይቅርታ የእኔ መቤት ስለደረሰብሽ በደል በነሱ ላይ ግን አስተዳደራዊ እርምጃ እንወስዳለንየሀላፊው ንግግር ነበር፡፡አዎ ግዴታችሁ ነውየኔ መልስ ነበር ፡፡
በሳምንቱ
በደርጅታችን በኩል በነዛ ጥበቃዎች ላይ የተወሰደውን አስተዳደራዊ እርምጃ የሚገልጽ ዳብዳቤ ደረሰን፡፡አሁን ተካስኩ አልኩኝ፡፡ትንሽም ቢሆን ከስህተታቸው የተማሩ ይመስለኛል፡፡
እናም እንዲህ ስል አሰብኩኝ፡፡እስከመቼ ይሆን ሰውን በቁመናው፤በአለባበሱ፤በቦርጩ ፤በውፍረቱና መሰል ከሰው ስብዕና ጋር ምንም ተገአቦት በሌላቸው መስፈርቶች መፈረጅና መመዘን የምንተወው?ይሄ ጉዳይስ ከአፓርታይድ በምን ይተናነሳል፡፡ግርም የሚለው ደግሞ የእኛው አፓርታይድ እየደረሰብን ያለው በራሳችን ዜጎች መሆኑ ነው፡፡የሌሎቹስ በነጮቹ ነበር፡፡እኛ ባዶ እጃችንን ሆነን እንዲህ ስንበረበር በሌላ በኩል ደግሞ ምናልባትም ለደህንነት ስጋት የሆኑ ነገሮች የተሸከመ አንድ ፈረንጅ አንድም ጥያቄ ሳይጠየቅ ሰተት ብሎ ይገባል፡፡አይ የኛ ነገር ግራ እኮ ነው ሁሉ ነገራችን፡፡እነሱ ጋር ለደህንነት ከሆነ በቃ ነጭ፤ ጥቁር ፤አርንጓዴ የለም….በቃ ሁልሽም ትበረበሪያለሽ ወይም አትበረበሪም …አለቀ!!
እንደዉም ፈረንጆቹ የራሳችንን ዜጎች እየበረበርን እነሱን ስናሳልፍቸው ምን እያሉ ሙድ እንደሚይዙብን ታውቃላችሁአዳሜ መስሎሽ ነው፤ምን እንደያዝኩ አላረፍሽም …Don’t Judge a book by its cover” hahaha…. የሚሉን አይመስላችሁም፡፡
እናም እባካችሁ
እነሱ እንዲህ ይላሉ “Please don’t judge a book by its cover”…መጽሀፉን በሽፋኑ አትገምግሙት፡፡ጥሩ ነውም መጥፎ ነውም ለማለት መጀመሪያ አንብባችሁ ተረዱትእንደማለት ይሆን፡፡
ቆዳው ስለነጣ ብቻ አትመኑት በአግባቡ ፈትሹት ስለጠቆርንና ስለቀጨጭን ደሞ ጋራዥ እንደገባ መኪና ሞተር መፍታት እስኪቀራችሁ አትበርብሩን ሀሳባችንንም ሳይቀርእባካችሁ ሚዛናዊ ሁኑ፡፡






kuku. A eb እዚሁ ፌስቡክ ላይ በመጻፍ ይታወቃሉ! በሙያቸው ጠበቃ ሲሆኑ የሚያነሷቸውን ማህራዊ ሃሳቦች የሚተቹበት ገጽ አላቸው….እነሆ አድራሻው!  https://www.facebook.com/kuku.eb ኢሜላቸውን ከፈለጉም እነሆ! kuku.eb@facebook.com