Total Pageviews

Wednesday, June 5, 2013

ስሜን ያየ!

ዝም ብሎ መተራመስ ምንድነው?
የአዲስ አበባን ውሎ ማወቅ የፈለገ በስራ ቀን ቢሮ መግባቱን ትቶ አንዱ ኢንተርኔት ካፌ ጎራ ይበል፡፡ ለካ ስንት ነገር አምልጦኛልና የሚል ቁጭት ይፈጠርበታል፡፡ ትላንት ሰኞ ግንቦት 26 በእረፍት ስም ቢሮ ሳልገባ ብውል ሀገሪቱን እና ህዝቦቿን ስታዘባቸው ዋልኩ፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ ከሳምንታት በፊት ባንክ ሄጄ መታወቂያዬን አዩና ሌላ የሚረባ መታወቂያ ካለሽ አምጪ ይሄኛው ሳይታደስ 2 ዓመት ያለፈበት ነው ተባልኩ፡፡ መቼ ወደ ቀበሌ መሄድ እንዳለብኝ የመከረኝ ደህና ዘመድ ስላልነበረኝ ከዛሬ የተሻለ ቀኝ አላገኝም አልኩና ሰኞ ወደ ከሰዓት በኋላ ከቤት ወጣሁ፡፡ አስቸኳይ  ፎቶ ተነሳሁ፡፡(‹አስቸኳይ ፎቶ አለ?› ተብለው ሲጠየቁ ‹አለ ግን ለዛሬ አይደርስም› የሚሉ ፎቶ ቤቶች አሉ ብለው ካሳቁኝ ሳምንት አልሞላውም፡፡ የኔው ከ35 ደቂቃ በኋላ የሚደርስ ነበር) እስከዛው ኢንተርኔት ካፌ ልቆይ ወሰንኩ፡፡ ቤቴ ለፎቶ ቤቱ ይቀርባል፡፡ ኢንተርኔት ካፌው ደግሞ ለፎቶ ቤቱ ይቀርባል፡፡ ከኢንተርኔት ካፌው በቅርብ ርቀት ላይ ውዱ ቀበሌአችን ይገኛል፡፡
ሳላስበው ለአንድ ሰዓት ተኩል አካባቢ በኢንተርኔት ካፌው ስቆይ ሰዎች እየመጡ እንዲህ ይጠይቁ ነበር፡፡
‹ስሜን ታዩልኛላችሁ?›
< ፎቶ ኮፒ አለ?›
‹  መመሪያውን ታሳዩኛላችሁ?›
‹ፎቶ ኮፒ›
‹የኮንዶሚኒየም ምዝገባ ካርዴ ይኸው! ስሜ - - -›
ወጣት ሴቶች፣አሮጊቶች ሽማግሌዎች፣ጎልማሳ ወንዶች  - - - ከኢንተርኔት ጋር ትውውቅ የሌላቸው ግራ የገባቸው ዜጎች ኢንተርኔት ካፌዋን በስራ እና በጥያቄ ብዛት ወጥረዋታል፡፡ ሲያቀብጠኝ ብዙ ሊያቆየኝ የሚችል ኮፒ የሚደረግ ጉዳይም ይዤ ነበር የሄድኩት፡፡በየጣልቃው የቤት አዳኞቹን ፎቶ ኮፒ ስለምትሰራ ካሰብኩት ትንሽ አቆይቶኛል፡፡ በቃ ኮፒው እስኪያልቅ ፎቶዬን ይዤ ቀበሌ ደረስ ብዬ ልምጣ አልኩና ሄድኩ፡፡
ቀበሌው በሰው ብዛት ጢም ብሏል፡፡በፊት መታወቂያ  የሚታደሰው አዲስ በተገነባው የቀበሌው ፅህፈት ቤት ህንፃ ላይ ፤በአንድ መስኮት፤ 5 ደቂቃ ላልበለጠ ጊዜ በሚሰጥ አገልግሎት ነበር፡፡ አሁን ከፎቁ ወርደው በአንድ ነባር አሮጌ አዳራሽ ወርደዋል፡፡‹ወደ ህዝቡ ቀረብ እንዲሉ ነው› ብላ ቦታው የተለወጠበትን ግምቷን ያካፈለችኝ ሴት ነበረች፡፡ አዳራሹ ውስጥም ከአዳራሹ ውጪም ሰው እንደጤፍ ፈሷል፡፡
‹ምንድነው ይሄ ሁሉ ሰልፍ?› አልኩ
‹መታወቂያ  ለማሳደስ›
‹እስከዛሬ የት ከርመው ነበር?› አላልኩም፡፡ እኔ ራሴ የት ከርሜ ነበር?
የሰልፍ ቁጥር ደግሞ ይታደላል፡፡ 68 ሰዎች ቀድመውኛል፡፡ 69 ቁጥርን ተቀብዬ በማግስቱ ለመመለስ ቁጥር ወደሚሰጠው ሰው ሄጄ ስጠይቀው፡፡ ‹ቆይ ወረፋ ይዘሽ ጠብቂ የተሰጠው ቁጥር ሲያልቅ ነው አዲስ የምንሰጠው› አለ፡፡ ህዝቡን እንዳሻው ሲያደርገው አሳላፊው ፊት ላይ የነበረው ደስታ ልጁን የሚድር እንጂ መታወቂያ ለመውሰድ የመጣ ሰው የሚያሰልፍ አይመስልም፡፡ የቀበሌው ጊቢ ውስጥ ትዳር አለመያዛቸውን ለማስመስከር በሚሯሯጡ ሰዎችም ተሞልቷል፡፡ ‹እንደዚህ አይነት ሰርግና ምላሽ ውስጥ መቆየቱ አያዋጣኝም› አያልኩ በውስጤ እያልጎመጎምኩ ፤ግርግሩ እስኪበርድ ወደ ቀበሌ ድርሽ እንደማልል ለራሴ ቃል እየገባሁ ወደ ኢንተርኔት ካፌው ተመለስኩ፡፡
የኢንተርኔት ካፌው ባለቤትና የኔን ኮፒ እያደረገች የዛን ሁሉ ሰው ጥያቄ ስታስተናግድ የነበረች ልጅ በወሬ ጠመድኳት፡፡
‹እኔ የምልሽ ምንድነው ትርምሱ?›
‹10 በ90 እና 20 በ80 ቤት ለመመዝገብ የባንክ አካውንት ክፈቱ ተብሏል›
‹ታዲያ ስማችንን እዩልን የሚሉት ለምናቸው ነው?›
‹ ከዚህ በፊት ኮንደሚኒየም የተመዘገቡት ናቸው፡፡ ቢጫ ካርዷን ይዘው ይመጡና ስማችንን እዩልን ይላሉ፡፡ እሱ ዝርዝር ደግሞ እኛ ጋር አይገኝም፡፡›
‹የት ነው የሚገኘው?›
‹እኔጃ! እዛው ቤቶች ልማት ይሆናል፡፤ ኢንተርኔት ላይ መኖሩንም የነገረን የለም›
‹ለምንድነው ስማቸውን የሚፈልጉት?›
‹ይጠፋል አሉ›
‹ወዴት ይጠፋል?›
‹በቃ ይጠፋል፡፡ እልም እልም ብሎ ይጠፋል፡፤የእኔ እህት አሁን ከተመዘገበችበት ስሟ ጠፍቷል፡፡ እንዳትከስ ደግሞ ቢጫ ካርዷን አጣችው›
‹ታዲያ የአዲሱ ምዝገባ ዕለት እዛው ሄደው ጠይቀው ጠፍቶ ካገኙት ከመንግስት ጋር አይነጋገሩም እንዴ?›
‹ እኔ ምን አውቃለሁ ሰው ዝም ብሎ መተራመስ ይወዳል፡፡ አሁን ቅድም የመጣቸውን ሴትዮ አይተሻታል? ጠዋት 3 ሰዓት ላይ ስሟን ፍለጋ ስራ አቁማ ከቢሮ የወጣች እስካሁን ሳታገኘው ይሄው 9 ሰዓት ሆነባት፡፡ ተይ ስምሽን ኢንተርኔት ካፌ አታገኚውም ብንላት የቤት ዕጣዋን የወሰድንባት ይመስል እንደጠላት አየችን፡፡ ደግሞ ለዛ ውሀ ላይ እየተተከለ ለሚሰምጥ ቤት፡፡ ሁለት ኮንደሚኒየም እኮ ሰምጧል አልሰማሽም?››
‹ከሰማሁ ቆይቻለሁ፡፡ ግን እኔ ዘንበል እንዳለ ነው የቆምኩት መስመጡን አልነገሩኝም፡፡ - - -እኔ የምለው ግን ፤እናንተ ዛሬ ስራ የበዛባችሁ ምን እየሰራችሁ ነው?›
‹የባንኩን ፎርም እና መታወቂያ ፎቶ ኮፒ እናደርጋለን፡፡ መመሪያው ደግሞ ፋና ዌብሳይት ላይ አለ እሱን እናሳያለን፡፡ምን እንደሚያስፈልግ ዌብሳይቱ ላይ ቁልጭ ብሎ ተቀምጧል፡፡ እሱን ቢያዩኮ መቼ መምጣት እንዳለባቸው ስለሚያውቁ ግርግሩም ትንሽ ቀነስ ይል ነበር፡፡ለምሳሌ የ40በ 60 ምዝገባ ገና ነሀሴ ላይ ነው፡፡ ሰው ግን ግርግርና መንሰፍሰፍ ይወዳል፡፡›አለችኝ እንግፍግፍ እያለች፡፡
‹እስኪ ለኔም አሳዩኝ› አልኳት፡፡ አንዱ የኮምፒውተር ስክሪን ፊት አስቀመጠችኝ፡፡ ለነባር(ከዚህ በፊት ኮንደሚኒየም ዕጣ ላይ ለመግባት ለተመዘገቡት) እና  ለአዲሶች ተብሎ ተለይቷል፡፡ አዲስ ተመዝጋቢ ሲኮን በየወሩ የሚቀመጠው ተቀማጭ ከነባሮቹ ይቀንሳል፡፡ ቀደም ብዬ የሰማሁት ቢሆንም የኢንተርኔት ቤቷ ልጅ የተረዳችውን እንድትነግረኝ ጠየቅኳት፡፡
‹መዋጮው ለአዲሶቹ የሚቀንሰው የቤቱ ዕጣ በቶሎ ስለማይደርሳቸው ነው፡፡ 7 ዓመት መጠበቅ አለባቸው፡፡ አዲሶቹ  በሚያስቀምጡት ብር ነው ለነባሮቹ ቤት የሚሰራው፡፡ ነባሮቹ የዛሬ 5 ዓመት የቤት ባለቤት ይሆናሉ፡፡ ነባሮቹ ልክ ቤታቸው እንደገቡ ደግሞ በሚከፍሉት ብር ለአዲሶቹ ቤት ይሰራላቸዋል፡፡›
‹ነባሮቹ ቤታቸውን ከተረከቡ በኋላ ለምን ይከፍላሉ አስቀመጡ አይደል እንዴ 5 ዓመት ሙሉ?› አላዋቂነቴ ሳይገርማት አልቀረም
‹እንደ ተቀማጩ እኮ 50 ፐርሰንት ነው፡፡ የት ነበርሽ አንቺ ይሄ ሁሉ ሲወራ?›
ምሳ ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ቴሌቪዥን ለነባር ተመዝጋቢዎች ፣ ለሴቶች ለመንግስት ሠራተኞች ቅድሚያ እንደሚሰጥ ሰምቻለሁ፡፡ እንዲህ እያወራን አንድ ሰውዬ መጣ፡፡ ‹እስኪ የኮንደሚኒየም ዕጣ እዩልኝ› አለ፡፡ፊቱ በደስታ በርቷል፡፡
‹አዲስ የኮንደሚኒየም ቤት እጣ አለ እንዴ?› አልኩ መቼም መጠየቄ ካልቀረ የሚሰራ የሚወራውን ሁሉ ልወቅ የሚል ዘመቻ የያዝኩ ይመስላል፡፡
‹በመጨረሻ የወጣው ነዋ›
‹መቼነው እሱ የወጣው? ይቅርታ ከዚህ በፊት ስላልተመዘገብኩ ዕጣ ሲወጣ ጉዳዬ ብዬ አልከታተልም ፡፡› አልኳት፡፡
‹ያኔ ነዋ የምርጫው ሰሞን?›
‹የቱ ምርጫ?›
‹የኢህአዴግ ምርጫ ነዋ! ልክ ምርጫው ሲቀርብ እኮ ነው የወጣው› አለች
‹እኮ ታዲያ እሱ ዕጣ አልቆየም እንዴ?›አልኩና ከጨዋታ ውጪ መሆኔን ለመሸፈን ዕጣው እንዲታይለት የፈለገውን ሰው ወደ ጨዋታው እንዲህ ስል አስገባሁት፡፡
‹አንተ እስከዛሬ እንዴት ዕጣውን ሳታይ ቆየህ?›
‹ሰዎች የኮንደሚኒየም ዕጣ እንደደረሰኝ ነግረውኝ፡፡አላምን ብዬ አይቼው አሁንም በድጋሚ ኢንተርኔት ቤት ቀይሬ ላየው ነው፡፡›
‹እንኳን ደስ ያለህ፡ ግን ለምንድነው ደጋግመህ የምታየው ዕታ ከወጣ በኋላም ስም ይጠፋል?›
‹ሳይሆን እኔ አልተመዘገብኩም ነበራ!›
‹ምን?!›
‹ሙች! ለሴት ቅድሚያ ይሰጣል ብለን ሚስቴ ነበረች የተመዘገበችው፡፡ ሁልጊዜ ዕጣ ሲወጣ የሷን ስም ነው የምንፈልገው፡፡ አሁን እኔን ደረሰህ አሉኝ ስሜ እስከነ አያቴ እስከ አድራሻዬ እኮ ነው ቁልጭ ብሎ የተገኘው፡፡ምንም ስህተት የለበት፡፡›
‹ቢጫዋ ካርድ አለችህ?›
‹የለችኝም፡፡ አልተመዘገብኩም እያልኩሽ?›
‹ሌላ ሰው ተመዝግቦልህ ይሆናል፡፡›
‹ማንም አልተመዘገበልኝ፡፡ ደግሞስ ለሰው መመዝገብ ይቻል ነበር እንዴ?›
‹ታዲያ እንዴት ሊደርስህ ይችላል? ወይ የሆነ የሄድክበት አቋራጭ መንገድ ይኖራል፡፡›
መሀላውን ደረደረ፡፡ እኔ ጭንቅላት ውስጥም እንዲህ እንዲህ እያሉ ጥያቄዎች ተደረደሩ፡፡ ሰዎች የሆነ የሰሙት ነገር ሳይኖር መቼም ስማቸውን ፍለጋ ኢንተርኔት ቤት ለኢንተርኔት ቤት አይንከራተቱም? የኮንደሚኒየም ተመዝጋቢዎች ስም በኢንተርኔት ላይ ይገኛል አይገኝም? ሰዎች ተመዝግበን ስናበቃ ስማችን እየተሰረዘ ጠፋ እያሉ ይጨነቃሉ፡፡ እውነት ነው ውሸት? መቼም ላም ባልዋለበት ኩበት አይለቀምም እሳት በሌለበትም ጭስ የለም፡፡ አንድ ሰው ሳይመዘገብ የኮንደሚኒየም ዕጣ የሚደርሰው እንዴት ባለው ተዓምር ነው? ተመዝግቦ 10 ዓመት ቤት ከመጠበቅና ሳይመዘገቡ ተዓምር ከመጠበቅ የቱ ያዋጣል? እሺ መንግስት ራሴ ሰርቼ ነው የምሰጣችሁ ብሩን ለኔ ስጡኝ ከዛ ዕድሜ ዘመናችሁን ቤት እያላችሁ ጠብቁኝ ማለቱን ይበል የሚሰለፍለት ካገኘ እሰየው፡፡ ግን ሰፋ ያለ የመመዝገቢያ ጊዜ ገደብ መስጠት(ልክ የምርጫ ካርድ እንደመውሰድ ያለ በጠዋት ቤት ለቤት እየዞሩ ‹የመጨረሻው ቀን ቀርቧል› እያሉ እንደሚቀሰቅሱት ዓይነት)፣ከምር ቤት የቸገረውን ለይቶ መስጠት፣መሬት ሰጥቶ እንደፈለጋችሁ ስሩ ማለት አይችልም ነበር?
‹አንቺ ግን እንደባለፈው እንዳያመልጥሽ አሁን ተመዝገቢ፡፡በኋላ እንዳይቆጭሽ፡፡› አለችኝ ስወጣ ጠብቃ

እኔ ለራሴ ገና ጥያቄ ላይ ነኝ፡፡ ብር ብሎ ተነስቶ እንደሚሰለፍ ህዝብ ብዙ ነገር አልገባኝም፡፡ ጥያቄ - ጥያቄ  -ጥያቄ ፡፡ ጥያቄ አያልቅም፡፡



ጸሃፌ ተውኔት መዓዛ ወርቁን በሸገር የአልጋ በአልጋ ተከታታይ ድራማና በህይወት መሰናዶ ድራማ ደራሲነታቸው እናስታውሳቸዋለን፡፡ አሁን እየታየ የሚገኝ ዝነኞቹ የተሰኘ ቴአትርም አላቸው፡፡ አስተያየት ካላችሁ በፌስቡክ አድራሻቸው በኩል በhttps://www.facebook.com/meaza.worku.39 ሊያገኙዋቸው ይችላሉ፡፡

1 comment:

  1. ተመዝግቦ 10 ዓመት ቤት ከመጠበቅና ሳይመዘገቡ ተዓምር ከመጠበቅ የቱ ያዋጣል? Good view

    ReplyDelete