Total Pageviews

Wednesday, July 17, 2013

"ትሻልን ሰድጄ ትብስን አመጣሁ!"


በአንዲት ገጠር ከተማ የሚኖር አንድ ሰው ነበር አሉ፡፡  
ሰውየው መቃብር እየፈነቀለ ትኩስ አስክሬን አየጎተተ አውጥቶ መልሶ ይቀብራል፡፡ ግን ደግሞ የለበሱትን ልብስ ያጌጡበትን ጌጥ የደረቡትን ኩታ እያወጣ ይዘንጥበታል፡፡

ለዚህ ሰው የአንድ የአከባቢው ሰው ሞቶ እናም ተቀበረ ማለት ሀዘን ሳይሆን የደስታ ምንጭ ሆነ፡፡ ሰው ይሞታል ይቀበራል እሱም ሬሳውን አውጥቶ ልብሱንና ጌጡን ገፎ መልሶ ይቀብራል፡፡ ህዝብ ተማረረ፡፡ የፍትህ ያለ ቢልም መፍትሄ የሚሰጥ ጠፋ፡፡

መቸም ሰው ሆኖ ከአፈር የሚቀር የለምና ይህ ነውጠኛ ህዝብን ያስነባ ሰውም ተራው ደርሶ ሞተ፡፡ ፌሽታው በተራው የህዝቡ ሆነ፡፡ የአከባቢው ሰው ሆ ብሎ ደስታውን ለመግለፅ በነቂስ ወጣ…ስለቴ ሰመረ ያለ ፤ ወደ ፈጣሪው ያንጋጠጠም ብዙ ነበር፡፡ የሀዘን ሳይሆን የሰርግና ምላሽ ቀን መሰለ፡፡ በዚህ ሁሉ ውስጥ በሚያየው ነገር ያዘነና የተቆጨ አንድ ሰው  ነበር፡፡ እሱም የሟቹ ብቸኛ ወንድ ልጅ ነው፡፡
                        
                   ልጅ የአባቱን ስም በመልካም ሊያስጠራ ዛተ፡፡ ጭካኔው ግን ከአባቱ ከፋ፡፡

የተቀበረ አሰክሬን እያወጣ የፈለገውን ይወስዳል አስክሬኑን ሳይመልስ እንኳ ባለበት ጥሎ የሄዳል፡፡ ተቀበሩ የተባሉት ሰዎች አስክሬን አመሻሽ ላይ በጅብ እየተጎተተ የተለያየ  የሰውነት ክፍላቸውም ከነዋሪው ደጅ ላይ ሁሉ ይጣል ጀመረ፡፡ ሕዝብ እግዚኦ ፈጣሪ ምኑን ላከብን ሲል ኡኡታውን አለ፡፡ ኧረ አባቱ በምን ጣዕሙ እሱው ይሻል ነበር ቢያንስ እሬሳውን መልሶ አፈር ሳያለብስ አይሄድም ነበር ተባለ፡፡

                                ልጅ ዝቶም አልቀረ፡፡ አባቱን አስመሰገነ፡፡

ጡረታ የወጣሁ መምህር ነኝ ያሉ አንድ አባት ናቸው ያጫወቱኝ፡፡ አሳቸው የፈለጉትን ጉዳይ ለማስረዳት ተጠቀሙበት እኛ ደግሞ በታሪክ ፈረስ ጋልበን ዛሬ ላይ እንምጣ፡፡

ኢትዮጲያ በተለያየ ስርዓት እና  መንግስታት ስር አልፋ ዛሬ ላይ ደርሳለች፡፡ የስርዓትም ባይሆን በየግዜው የተለያዩ አዳዲስ የወንበር ለውጦች መደረጋቸውን ይሰማል ይታያልም፡፡ አዲስ ጠቅላይ ሚንስትር አይተናል፡፡ ከሰሞኑ እንኳ ወሬው ሁሉ ሹመትና ሽረት ሆኗል…አዳዲስ ሚንስትሮች ፤ አማካሪዎች ፤ ከንቲባ ሌላም ሌላም፡፡

ስልጣኑን በሙስና ተዘፍቋል ተብሎ የተነጠቀ አለ፡፡ በአቅም ማነስ ፤ ከአንዱ ወደ አንዱ ለማገለባበጥ ታስቦ የተነሳ እና ቦታ የቀየረም አለ፡፡ ስራ ዘመኑን አጠናቆ የተሰናበተም አለ፡፡ ለኛ የማይታይ ምክንያትም ይኖር ይሆናል፡፡

እገሌ ሄዶ እገሌ ቢመጣም በአንድ ነገር እንግባባለን ፤ ህዝብ ሁሌም ከትላንት የተሻለውን ለዛሬው ይመርጣል፡፡ ይገባዋልም፡፡
የባሰበት ደም መጣጭ ርሃብተኛ አያ ጅቦ ሌቦ ቦጥቧጭ ፤ ከእጅ አይሻል ዶማ የሆነ የአቅም ውስንነት  ያለበት የሚሰራውን በውል የማይችል አስተዳዳሪ ከሆነ ተመስገን ሳይሆን የትላንቱን አምጡልኝ ያስብላል፡፡ገና ምን አየህ ተብሎ ለእንካ ቅመስ እጅጌ መሰብሰብም ነገ ያስተዛዝበናል፡፡

አዳዲሶች መሪዎቻችን ከቀደምቶቹ ስህተት ሊማሩ እና ሊያርሙ ይገባል እንጂ መሳ ለመሳ በፈሰሱበት ሊፈሱ አይገባም፡፡ የሱ ወይም የሷ ግዜ ተብሎ የምንዘክርላቸው አዲስ ሃሳብ አዲስ አሰራር አዲስ ለውጥ እንዲያሳዩን ከወዲሁ እጃችሁ ከምን ብለናል፡፡

ጥሎብን ይሁን ተጥሎብን ባላውቅም ዘመናችን ዝምታ ያይልበታል፡፡ ወንበር የሰጠናቸው ሰዎች ግን ንግግራችንን ብቻም ሳይሆን ዝምታችንም የሚገባቸው ሊሆኑ ይገባል፡፡

                                              ሰላም!


ጋዜጠኛ ሃኒ ሰለሞን ከሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በውጭ ቋንቋዎችና ስነጽሁፍ በመጀመሪያ ድግሪ ተመርቀዋል፡፡ አሁን በሸገር ኤፍ.ኤም ሬዲዮ በጋዜጠኝነት በመስራት ላይ ይገኛሉ፡፡ ሃሳብና አስተያየት ካለዎት በኢሜላቸው honeysolomon123@yahoo.com በፌስቡክ ገጻቸው https://www.facebook.com/honey.solomon.3 ሊያገኟቸው ይችላሉ፡፡

3 comments:

  1. Thomas Edison tried two thousand different materials in search of a filament for the light bulb. When none worked satisfactorily, his assistant complained, “All our work is in vain. We have learned nothing.”

    Edison replied very confidently, “Oh, we have come a long way and we have learned a lot. We know that there are two thousand elements which we cannot use to make a good light bulb.” they should learn from their mistake.it is good if it isn't happen!good article u wrote honey!!

    ReplyDelete
  2. ዛፍ የቆረጠኝ ብረት ሳይሆን እንጨት ነው አለ፡፡

    ReplyDelete