Total Pageviews

Wednesday, July 10, 2013

"ቦሌ እና ጉለሌ ወይም ሌላ…"

እህሳ እንዴት ሰነባብታችዋል?
የሰሞኑ ወሬ ሁሉ
ፖለቲካ ….ፖለቲካ…
ሹመት…ሹመት….
ሽረት….ሽረት….
ከንቲባ…ከንቲባ ምናምን ሆኗል፡፡ የሹም ሽሩን ነገር "ጉልቻ ቢለዋወጥ…" ነው፡፡ የቤት ምዝገባው ነገር አሁን ላይ ጋብ ያለ ይመስላል፡፡ ደግሞ ነሀሴ ገብቶ እነ 40/60 ሽር ጉድ እስኪሉብን፡፡
"መጀመሪያ የመቀመጫዬን አለች ዝንጀሮ" አሉ? እኔ አሁንም ቀልቤ ከቤቱ ላይ ነው፡፡
በአዲስ አበባ ቤት ከግድግዳ እና ጣሪያም በላይ ነው፡፡ መቼም የኮንዶሚኒየም ቤት እጣ ተጀመረ ብሎ 80ውን ለመቅደድ ህሊናው የሚፈቅድለት ሰው ሲታይ እንዲህ ብሎ መናገር ያስደፍራል፡፡
ቤት የማይነጥፍ ላም ነውና ሁሉም ሊኖረው ቢኖረውም ለመጨመር ለመጨማመር ያስባል፡፡ ምክንያቱም ቤት ነው፡፡ ከተማዋ ደግሞ አዲስ አበባ…
በርግጥ የችግሩ ስፋት ምንም ያስኮናል፡፡
ቆየት ቢልም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከ 5 ዓመት በፊት የተሰራን ጥናት ብነግራችሁ ጨዋታዬን ያሳምረዋል፡፡ በቤት ቁጥሩ ላይ መሻሻል ይኖራል ብለን ብናስብ እንኳ ሰውም የዚያኑ ያህል ተሰግስጓልና ችግሩ  ቢብስ እንጂ ያገግማል የሚል ሃሳብ መስጠት ይከብዳል፡፡
በአዲስ አበባ ከሚገኙ ቤቶች 84.4 በመቶ ያህሉ መኖሪያ ናቸው ቢሆንም ከቤት ፍላጎቱ አንጻር ይህ ቁጥር 60 በመቶ ገደማ እንኳ አይሸፍንም፡፡ በከተማዋ ካሉት መኖሪያ ቤቶች መጪውን 20 ዓመት ሊሸጋገሩ የሚችሉት ደግሞ 35 በመቶው ብቻ ናቸው፡፡
እነዚህ ቤቶች ቤት መባላቸው ብቻ ለኑሮ የተመቹ የሚለውን የሚወክል አይደለም፡፡ የማእከላዊ ስታትስቲክስ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት በከተማዋ ከሚገኙ መኖሪያ ቤቶች 75 በመቶው መፀዳጃ ቤት እና 26 በመቶው ማድ ቤት የሌላቸው ናቸው፡፡ ከ30 በመቶ በላይ የሚሆኑት ደግሞ ባለ አንድ ክፍል  ናቸው፡፡
ታሪክን የኋሊት
ቀድሞ አዲስ አበባ ስትቆረቆር የደጃዝማች ፤ የራስ እገሌ ሰፈር እየተባለ የጦር አለቆቹ በስራቸው ያሉትን እያስተዳደሩ ትኖር ነበር ይላሉ የታሪክ ሰዎች፡፡
ከዛማ ጣሊያን ገባ ፒያሳ እና ካዛንቺስ የመደብ ልዩነትን አመጡ፡፡ የሮም ሰዎች ካዛንችስን ለመኖሪያቸው ፒያሳን መገበያያቸው ሲያደርጉ መርካቶ…'ተራ' ተብለው ለተጠሩት አባት አያቶቻችን ለመገበያያነት  ተዘጋጀች፡፡
ጣሊያን ጥፋቷ ሳይበዛ ቶሎ ለቃ መውጣቷ እንዲሁም በቅኝ ግዛት አለመውደቃችን የነጭ የጥቁር ወይም በሃይማኖት ልዩነት የተከፋፈለ አኗኗር እንደሌላው የአፍሪቃ ሀገር ጎልቶ እንዳይወጣ ቢያደርግም በከተማችን እንዲህ አይነቱ የኑሮ መደብን መሰረት ያደረገ አከታተም ብቅ ካለ ሰነባብቷል፡፡
አሁን በአዲስ አበባ የሀብታምና የደሀ ሰፈር አለ፡፡ የተራራቀ የሀብት ልዩነትም እንዲሁ፡፡ በአዲስ አበባ ድሃው ህዝብ በቪዛ እንደሚሄድባቸው ሃገሮች ሩቅ የሚመስሉት ቢሄድም ባይተዋረኝነት እንዲሰማው የሚያደርጉ ሰፈሮች ፤ ሀብታሙ ደግሞ ቀልድ አዋቂ ነን የሚሉ ሙያተኞች ሲቀልድባቸው ከመስማት ውጭ በውል የት እንዳሉ እንኳ በርግጠኝነት የማያውቃቸው ሰፈሮች ተበራክተዋል፡፡
በሪል ስቴት መንደሮች የቤቱ ቀጥተኛ ነዋሪ ካልሆኑ ወይም ቀድሞ እኔጋ እሚመጣ እንግዳ አለ ብሎ ስምዎን ከዘቦቹ የሚያስመዘግብ ሰው ከሌለ በቀር እንዲሁ ዘው የማይባልባቸው በጥርብ ድንጋይ የታጠሩ አደገኛ በሚል የኤሌትሪክ ሽቦ የተከለሉ ግቢዎች ብዙ ናቸው፡፡ በዚህ አከባቢ መኖር ብቻ አይደለም እምጠይቀው ዘመድ አለኝ ማለት የኑሮ ደረጃዎን ከፍ ያደርጋል፡፡
ቀድሞ ሪል ስቴት እና የጋራ መኖሪያ ቤቶች ወይም የኮንደሚኒየም ቤቶች ጉዳይ ነበር ለችግሩ መባባስ እንደምክንያት የሚነሳው፡፡
አሁን ደግሞ 10/90 ፤ 20/80፤ 40/60፤ ……… ተጀምሯል፡፡ ይህ አዲስ የቤቶች ፕሮግራም ቀድሞ የታሰበ እና ዝግጅት ያልተደረገበት መሆኑን የሚያሳብቁ ችግሮችን ገና ካሁኑ ማግተልተል ጀምሯል፡፡ መሰንበት ደጉ ገና ደግሞ ያሳየናል፡፡
የከፍተኛ ሀብታም ሰፈር፣ የመካከለኛ ሀብታም ሰፈር፣ መካከለኛ፣ የድሃ እና የፍጹም ድሃ ሰፈር ብሎ መከፋፈሉ ከዚህ ሰፈር ነኝ ማለት የሚያፍሩ ልጆች እዚህ ሰፈር ዘመድ አለኝ ብለው የሚጠይቃቸው ስጋ የሌላቸው ነዋሪዎችን እንዳይወልድልን ነዋሪውን የማሰባጠሩ ጉዳይ ላይ ከወዲሁ ሊታሰብበት ይገባ ነበር… ግን አልሆነም፡፡ እስካሁን ሲነገር የሰማነው የቦታ አደላደል ከፋፍለህ አሳድር አይነት ነው፡፡
10/90 የቤት ፕሮግራም በፍፁም ድህነት ስር ላሉ ዜጎች የተዘጋጀ ነው ተብሏል፡፡ ፕሮግራሙ መታሰቡ ጎሽ የሚያስብል ነው፡፡ ግን ደግሞ ቤቱ የት ይገነባል? እነዚህን ሰዎች አንድ ቦታ ላይ አጉሮ ማኖርስ አዲስ አበባ ከሌሎች አቻ ከተሞቿ ትሻላለች ያስባላትን የስብጥር ኑሮ አያጠፋው ይሆን የሚለውን ጥያቄ ያመጣል፡፡
አሁን ላይ ምዝገባው በተጠናቀቀው 10/90 የተመዘገበው ሰው ቁጥር ከታሰበውም ቀድሞ ከተጀመሩት የቤቶች ግንባታም ያነሰ ነው፡፡ 187 ብር በወር ቆጥቤ መንግስቴ ለምንዱባን ብሎ እሚሰራው ቤት ከምኖር 274 ብር ቆጥቦ በ20/80 የአንድ መኝታ ቤት ባለቤት ለመሆን ከ900 ሺህ ሰው ውስጥ የተአምር እድል መጠበቅ እመርጣለሁ የሚል ይበዛል፡፡ አሊያም የሰዉ የኑሮ አቋም መንግስት አያውቀውም ማለት ያስችል ይሆና፡፡ ዞሮ ዞሮ ግን በጥናት አልመጣም ያስብላል፡፡
ባለመካከለኛ ገቢው ባለ 20/80ው አንድ ላይ… ውጪ ቀመስ የሆነውን ዲያስፖራ እና ሀገር በቀሉን ባለ ገንዘብ አንድ መንደር ማጎሩ መዘዝ አለው ይላሉ የህብረተሰብ ሳይንስ ባለሙያዎች፡፡ አብሮ ካለመኖር ካለመተዋወቅ አለመተዛዘን አለመተሳሰብ በጠላትነት መተያየትን ያመጣል፡፡
ኢትዮጵያዊ ሲኖር የሌለው ባለው ይፅናናል፡፡ ሃብታሙም የተቸገረ መኖሩን ሲያውቅ ነው ተመስገን የሚለው፡፡
ድሃው ድርሽ የማይልባቸው ቢመጣ እንኳ ቀኑን ሙሉ ለባለጠጋው ጉልበቱን ሲሸጥ ውሎ የሚመለስባቸው ሰፈሮች በአንድ አንድ ሀገሮች አሉ ይባላል በአፍሪቃ፡፡
አዲስ አበባ የአፍሪቃም ነች ስንል ከደሃው እየነፈግናት አይደለም፡፡ አንተ የእንትን ሰፈር ልጅ ተብሎ የሚሰደብ፣ እኔ የዚህ ሰፈር ልጅ ነኝ እያለ ሌላው ቆዳውን የሚያዋድድባት ከተማ ልትሆን አይገባም፡፡
ቢታሰብበት አይበጅም?

ቸር ሰንብቱ!


ጋዜጠኛ ሃኒ ሰለሞን ከሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በውጭ ቋንቋዎችና ስነጽሁፍ በመጀመሪያ ድግሪ ተመርቀዋል፡፡ አሁን በሸገር ኤፍ.ኤም ሬዲዮ ጋዜጠኛ ናቸው፡፡ ሃሳብና አስተያየት ካለዎት በኢሜይላቸው honeysolomon123@yahoo.com በፌስቡክ ገጻቸው https://www.facebook.com/honey.solomon.3?fref=ts ሊያገኟቸው ይችላሉ፡፡

No comments:

Post a Comment