Total Pageviews

Wednesday, June 12, 2013

የተጣጣፉት ሜኑዎች


አንዱን ቀን ከሁለት የቅርብ ወዳጆቼ ጋር ምግብ ቢጤ ፈላለግንና ወደ አንዱ ሆቴል ገባን፡፡

የምርጫችን ምክንያት “ትላንት የበላነው ቆንጆ ምግብ አለ...ዋጋውም መልካም ነው” የሚለው የገበታ ሸሪኮቼ ምክንያት ነው፡፡

ከመግባታችን ትላንት በላን...በ70 ብር ይሸጣል ያሉትን ምግብ አዘዝን፡፡

አስተናጋጁ ጠረጴዛውን አፀዳድቶ ሜኑ ይዞ ከተፍ አለ፡፡

“ፍሬንድ ነገርንህ እኮ” አለው አንዱ ከመካከላችን ፤ አስተናጋጁ ደግሞ “ወዳጄ የዋጋ ጭማሪ ስለተደረገ ትስማሙ እና አትስማሙ እንደው ብታዩት ይሻላል ብዬ ነው” አስረዳ፡፡

ሜኑው ተገለጠ፡፡ እንዳለቀ ሱሪ የተጣጣፈ ይበዛዋል፡፡

ትላንት 70 ብር ተበላች የተባለችው ምግብም ለመልስ እንዳታስቸግር ድፍን 100 ሆናለች፡፡

ጠላታችሁ ክው ይበል!

እኔም እንዲሁ ነው ድንግጥ ያልኩት፡፡ በአንድ ቀን አዳር? ጬሂ ጬሂ ያስብላል፡፡
ግን በየት በኩል? ማንን ደስ ይበለው ብዬ? ዋጥ ማድረግ እየተቻለ፡፡

“ለምን?” አልነው አስተናጋጁን፡፡

አስተናጋጁ የሚገባበት ጠፍቶት “ምንም አላውቅም፡፡ ትላንት ከሰአቱን እረፍት ነበርኩ ዛሬ ስመጣ ዋጋ ማስተካከያ እንደተደረገ ሰማሁ” አለ ቁልጭ ቁልጭ እያለ፡፡
የፈጣሪ ያለህ! ለማን አቤት ይባላል?

ያን ቤት በንዴት ብቻ ለቀን ወጣን፡፡ እኔ በበኩሌ በዛው ቀረሁ፡፡

ወዳጆቼ አሁን አሁን በአዲስ አበባ ካፌዎችና ምግብ ቤቶች ቋሚ የሚባል ነገር ጠፍቷል፡፡
ትላንት ያገኛችሁትን አገልግሎትና ዋጋ ዛሬ እንደሚያገኙ ርግጠኛ መሆን ለብዙ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ከብዷል፡፡

ሜኑዎቻቸው እንደ አየር ጠባዩ አሁንም አሁንም ይቀያየራል፡፡

ከምግብ ዝርዝሮች ፊት ለፊት ያሉት የዋጋ ተመኖች በቁርጥራጭ ወረቀቶች ተለጣጥፈው የቀድሞ ይዞታቸውን ለቀዋል፡፡

የንግድ ቤቶቹ ባለቤቶች ዋጋ ለመጨመር የሚወስድባቸው ፍጥነት በላስቲክ የለበጡትን ሜኔዎች በወጉ ለመቀየር እንኳ ጊዜ የሚሠጥ አይደለም፡፡

ታሸገው ከሚሸጡት ውሃና ለስላሳ ጀምሮ ምግብ ፣ ካፌ አፈራሽ መጠጡ ፣ሻይን ጨምሮ ሃገር አማን አይደለም እንዴ በሚያስብል ፍጥነት ያሻቅባሉ፡፡

ጭማሪው ደግሞ እስቲ ይሁና ለማለት እንኳ ትዕግስት አይሠጥም፡፡ ሊያውም መጠኑ እንዳለ ካለ፡፡

አንዳንዴ ትላንት ወይም በዚህ ሳምንት የበላሁት ነው፣አንዱ ሁለት ሰው አጥግቦ ይመልሳል ያሉትን ምግብ ወዳጆን ሊጋብዙ ሲሄዱ ከርሶ አንጀት እንኳ ጠብ የማትል ኪኒን የምታክል የምትሆንበት አጋጣሚ ብዙ ነው፡፡ ያሸማቅቃል!

እንዲህ ያለውን ድንገቴ የዋጋ ጭማሪ በካፌው ላይ አነሳን እንጂ በብዙ ምርትና አገልግሎት ላይ የሚታይ ነው፡፡
መቼም እንደ ዜጋ ሁሉኑም ማስደንገጡ ባይቀርም ጭንቁ የሚበዛው የወር ገቢው ተቆጥሮ ለምትሠጠውና እዚህጋ ዋጋ ጨምሬ ላካክስ በማይለው ቅጥር ሰራተኛ ላይ ነው፡፡

የቤት ኪራዩ ሲንር ወርሃዊ የትምህርት ቤት ክፍያው ሲጨምር ዶላር እዚህ ገባ እየተባለ ብጣሸ ጨርቅ ለመልበስ የወር ደሞዝን ሲገዳደር ታክሲም መንገድ ግንባታው አንድ መታጠፊያ ጨመረብኝ ብሎ ሳንቲም ለመመንተፍ ሲሯሯጥ  መቆጣጠር የሚገባው ቢሮ ተቀምጦ “ህገ ወጥ ነው፡፡ ያስቀጣል” ከማለት ባለፈ ህግን መጣስ እንደሚያስቀጣ ሳያሳይ ሲቀር ተጐጂው ይህው ግብሩን ያለ አንዳች ሽርፍራፊ የሚከፍለው ደሞዝተኛ ነው፡፡

ቀነስ ብሎ የሚገዛው ነገር ያጣ ሠው፣ ግሸበቱ ቀነሰ ወደ አንድ አሀዝ ወረደ 6 በመቶ ገባ ገለመሌ ቢባል ቁጥር እንጂ ምን ትርጉም ሊሠጠው ይችላል?

ምክንያቱ ላይ ደግሞ እናውራ

እኔ እኛ ተጠቃሚዎቹን ከመውቀስ እጀምራለሁ፡፡

ዘመናችን እራሱ የተወደደ ነገር ሁሉ ትክክልና የሚሻል የመሰለበት ነው፡፡
የልባችንን የሚያውቁት ነጋዴዎቹም ዋጋውን ሰማይ ሰቅለው የእቃውን ጥራት በዋጋው ውድነት እንድንለካው በማዘን ያስቀምጡልናል፡፡

አንድ ከፈረንሳይ የመጣ ወዳጄ የካፌ ቢዝነስ ያበላል ተብሎ የከፈተውን ሬስቶራንት ልመረቅ ገና በ4ኛ ቀኑ ሄጄ የሱም ሜኑዎች ተለጣጥፈው ሳይ ተገርምኩ፡፡ “አንተም?” ብለው፡፡
“ምን ላድርግ ብለሽ ነው ቀድሞ ብሎ የወጣውን ዋጋ ያዩ ጓደኞቼ ቤትህን ርካሽና መናኛ ያስመስለዋል በል ቆልለው በለውኝ ነው” ብሎኛል፡፡

ቀድሞ የነበረውን ወጪ እና ገቢውን አሰልቶ ያተርፈኛል ብሎ የወሠነውን ሒሳብም መቀየር ያስፈለገው በዚሁ ምክንያት ነው፡፡  
በርግጥ አንድ ሰው የካፌና የምግብ ቤት አገልግሎት ልሰጥ ብሎ ስራ ሲጀምር የራሱ የሆነ ብዙ ወጪ አለው፡፡ የቤት ኪራይ ይከፍላል ሰራተኛ ይቀጥራል የጥሬ እቃ ወጪ ይጠብቀዋል፡፡ የመብራትና ውሃም ይቆርጣል… ሌላም ሌላም፤

ከነዚህ አገልግሎቶች የሚቀበለው ገንዘብ ግን በትክክል ለሚሠጠው አገልግሎት እና ለሚያገኘው ተገቢ ትርፍ ብቻ ነው ወይ? የሚለው ነው ጥያቄው፡፡

መሸቶ በነጋ ቁጥር ለሚጨምረው ዋጋ መሸቶ ሲነጋ የቤት ኪራይ እየጨመረ? የመብራትና የውሃ ዋጋ እየናረ? ለሠራተኞቹ ደሞዝና ጉርሻ እንዲሁም ጥቅማጥቅም እየሠጠ? ወይስ ሌላ?

አንድ ኪሎ ቲማቲም በ5 ብር ሲጨምር በአንድ ምግብ 15 ብር ሚቆነድደን ነጋዴ  ሲቀንስስ ይቀንሳል እንዴ?

ለተጣጣፉት የአዲስ አበባ ሜኑዎች ምን ምክንያት አንስቶ ማሳመን ይችላል?


                       ቸር ያሰማን!



ጋዜጠኛ ሃኒ ሰለሞን ከሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በውጭ ቋንቋዎችና ስነጽሁፍ በመጀመሪያ ድግሪ ተመርቀዋል፡፡ አሁን በሸገር ኤፍ.ኤም ሬዲዮ በጋዜጠኝነት በመስራት ላይ ይገኛሉ፡፡ ሃሳብና አስተያየት ካለዎት በኢሜላቸው honeysolomon123@yahoo.com በፌስቡክ ገጻቸው https://www.facebook.com/honey.solomon.3 ሊያገኟቸው ይችላሉ፡፡

4 comments:

  1. BERABO HANNY DESS YELALE EYESAKU NEW YANEBEBEKUTEGN.... ERE DEGEMO YEMAT KELEME KEYEREW YEMEGEBUN YEZETENA TERAT SASHSHELU WAGA CHEMARI ADERGENALE YEMELUTESE BECHA NEGROCH YEGERMALU MAN GA HADEN ABET ENDEMENELE NEW GERA YEGEBAN ABEKAHU CHERE ENSENEBET HAGERACHEN LEZELALEM TENURE

    ReplyDelete
  2. netsa gebiya mibalnger legn hononal biya alsibm alyam alhnewum ymeslegnal

    ReplyDelete
  3. I like your Blogs. you always express the people's heart beat. It's rediculous to see the overnight price change for no legitimate reason or their foolish thinking of making their business classy by just raising the price. Is Greed the new way of getting rich in Ethiopia? Is there really a consumer protection advocate agency in Ethiopia to protect consumers?
    Keep up your cool blogs. funny but have points

    ReplyDelete